2014 ኦክቶበር 12, እሑድ

ስለ ቤተ ክርስቲያን /አቅሌስያ/

ስለ ቤተ ክርስቲያን   /አቅሌስያ/

በእግዚአብሔር ፈቃድና ስምረት ከዓለም ሁሉ የተመረጠች የተሰበሰበች የአህዛብና የአይሁድ ቅሬታ ምንስ ልዩ ልዩ አባላቶች ቢኖሩባት በአንድ በክርስቶስ ሥጋ አንድ አካል የሆነች አንድ ፍጹም ምሉዕ አቅመ አካል ለመሆንም እስክትበቃ ድረስ በእግዚአብሔር ቃል ወደ ራስዋ ወደ ክርስቶስ የምታድግ ክርስቶስም የማዕዘኑ ራስ ሲሆን በነቢያትና ሐዋርያት መሠረት ላይ ምዕመናንዋ መንፈሳውያን ድንጋዮች ሆነው ለአንድ ቅዱስ ቤተ መቅደስነት የሚሠሩባት እግዚአብሔርም አስቀድሞ በልጁ መልክ ምሳሌ እንድትሆን ባቀደበት ገንዘብ በቃሉና በደሙ ታጥባ ቅድስትና ንጽሕት ሆና በመንፈስ ሙሽራነት በክርስቶስ ቀኝ ለመቀመጥ የተመረጠች የእስራኤል ዘነፍስ ማኅበር መንፈሳዊት ጽዮን የምትሆን አንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንዳለች  እናምናለን፡፡
ምንም እንን በሜዳዊ ሥርዓቶችዋ ምክንያት ገብተው በመቀላቀል መስለዋት የአፍ ክርስቲያኖች ወገኖች ቢታዩባት እግዚአብሔር አባላቶችዋን በሚያውቅበት ምስጢር የማትታይ ቤተ ክርስቲያን ከክርስቶስ  ጋር በመንፈስ በመያያዝዋ የመንፈስ ቅዱስ ማደርያ ስለ ሆነች በጋለና በተቃጠለ ፍቅር በውስጥዋ ያለውን የክርስቶስን ወንጌሉን ብርሃን በቃልና በአካሄድ በልብም ንብረት እየገለጸች ይህንን ዓለም የምታስተምር ቅድስት ናት ስንል እናምናለን፡፡
ቤተ ክርስቲያንም ስንል ኀሳቡን በእዚህ ላይ እንደተመለከትነው ስለ ትልቅና ስለ ትንሽ ሕንጻ ሳይሆን ስለ ምዕመናን አንድነት መናገራችን እንደሆነ ከኒቅያና ከሐዋርያት ሥርዓተ ሃይማኖት ጠቅሰን በሚከተለው እናስረዳለን፡፡
ወነአምን በአሐቲ ቅደስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላዕለ ኩሉ ጉባኤ ዘሐዋርይት ፡፡
 የሐዋ 2፡47
በሁሉ ዘንድ በምትሆን ሐዋርያት በሰበሰብዋት በአንዲት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን
እንዲሁም ሳዊሮስ ፡-

በሐዋርያት ስብከት አብያተ ክርስቲያናትና ምዕመናን ሁሉ ሐዋርያዊት ጉባኤ ቤተ ክርስቲያን ይሆናሉ፡፡እርስዋ ከአሕዛብ ሁሉ የተሰበሰበች በመንፈስ ቅዱስ የተቀደሰች የቅዱሳን ሐዋርያት ጉባኤ ቤተ ክርስቲያን ናትና፡፡ ብሎ አስረድቶ ተናግርዋል

2014 ሴፕቴምበር 28, እሑድ

ሕይወት ዕድል ወይስ ምርጫ




የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ዕድል ሰዎች እንደሚሰጡት ትርጉም እነርሱን አድራሻ አድርጐ የሚመጣ፣ ያላሰቡትና ያልጠበቁት በረከት፣ በመንገዳቸው ፊት ለፊት የቆመ ማዕድ ማለት ነው፡፡ ሕይወት ግን በቋሚነት የተዋቀረችው በዕድል ሳይሆን በምርጫ ነው፡፡ ሕይወት ዕድል አይደለችም የምንለው፡-

1.             ማንኛውም ፍጥረት በአጋጣሚ ስላልተገኘ፣
2.            እግዚአብሔር ትእዛዝን ለሰው በመስጠቱ፣
3.            የሰው ልጅ ተጠያቂነት ያለውን ሕይወት በመቀበሉ፣
4.            እግዚአብሔር በሰው ጥፋተኝነት ላይ ብይን መስጠቱ ነው፡፡

1.          ማንኛውም ፍጥረት በአጋጣሚ አልተገኘም

በእግዚአብሔር ዕቅድና ዓላማ የሚታየውና የማይታየው ዓለም ተፈጥሯል፡፡ በስህተት የተገኘ፣ ቀስ በቀስም በማደግ ለዚህ የደረሰ ፍጥረት የለም፡፡ ፍጥረቱ በራሱ ላይ ካለው ዓላማ እግዚአብሔር በፍጥረት ላይ ያለው ዓላማ ይበልጣል፡፡ በሕይወት ውስጥ ትልቅ ትርምስ የሚከሰተው በአጋጣሚ ያልተገኘውን ሕይወት በአጋጣሚ ስንኖረው ነው፡፡ ዕድል የምንለው አጋጣሚ፣ ራሱን በራሱ ለእኛ የናኘ ስጦታ ነው፡፡ እንዲህ የሚባል ቸር የለም፡፡ የስጦታ ሁሉ ባለቤት እግዚአብሔር ነው /ያዕ. 1÷17/፡፡ ሕይወትን ዕድል ስናደርጋት አጋጣሚ እናደርጋታለን፣ ከዚህ ሁሉ በላይ የእግዚአብሔርን ሰጪነት እንቃወማለን፡፡

2.         እግዚአብሔር ትእዛዙን ለሰው መስጠቱ

ሕይወት ረግጠን የምናያት ሳትሆን ዓይተን የምንረግጣት ናት፡፡ ዓይቶ ለመርገጥ ይረዳ ዘንድም እግዚአብሔር ትእዛዝን ለሰዎች ሰጥቷል፡፡ ሰዎች ጠጪነታቸውን፣ ሱሰኝነታቸውን ሳይቀር የ40ና የ80 ቀን ዕድሌ ነው ይላሉ፡፡ ጽድቅና ኃጢአት ግን ምርጫ እንጂ ዕድል አይደሉም፡፡ ሕይወት ወደ ወሰደችን የምንከተላት ሳትሆን ተምነን የምንጓዛት ናት፡፡ ለዚህም ትእዛዝ ተሰጥቶናል፡፡


3.         የሰው ልጅ ተጠያቂነት ያለውን ሕይወት መቀበሉ

ትእዛዝ የሚወጣው ሥልጣን ካለው አካል ነው፡፡ ሥልጣን ያለው አካል ደግሞ በትእዛዙ መሠረት ይጠይቃል፡፡ እግዚአብሔር ትእዛዝን ሰጥቷል፡፡ በዚህ ምክንያት ተላላፊ የሆኑትን አዳምንና ሔዋንን እንዲሁም ቃየንን ጠይቋል፡፡ ሕይወት ዕድል ብትሆን ኖሮ ተጠያቂነት ባልኖራት ነበር፡፡ የመጣብን ነገር ነው፣ የማንለውጠው ምርጫ ነው እያልን በኃጢአታችን በተዝናናን ነበር፡፡ ሕይወት ግን ተጠያቂነት ስላላት በዘፈቀደ የምንጓዝበት ዕድል አይደለችም፡፡

4.         እግዚአብሔር በሰው ጥፋተኝነት ላይ ብይን መስጠቱ

ዕድል የሚባል የማንፈልገውን በረከት የሚያጥለቀልቀን፣ ዕድል የሚባል የማንፈልገውን ኃጢአት የሚያሸክመን ነገር የለም፡፡ እግዚአብሔር መርጠን የምንከተለውን ሕይወት ሰጥቶናል፡፡ በዚህ ምክንያት እግዚአብሔር ለመልካም ሥራችንም ሆነ ለክፉ ሥራችን ብይን ይሰጣል፡፡ እግዚአብሔር ብይን የሚሰጠው ሕይወት ዕድል ሳትሆን ምርጫ ስለሆነች ነው፡፡

         ሕይወት የመዝራትና የማጨድ ሕግ ናት፡፡ ሰው የዘራውን ነው የሚያጭደው ሲባል ሁልጊዜ ለክፉ የምንጠቀምበት ነው፡፡ በመልካም ነገርም የምናጭደው የዘራነውን ነው፡፡ መልካም ነገርም ክፉ ነገርም ሁለቱም ዘር ነው፡፡ ዘር ከሆነ ሁለቱም ይታጨዳል፡፡ በመዝራትና በማጨድ ድንጋጌ ውስጥ ሦስት ቋሚ ሕጐች አሉ፡-
1.             የዘራነውን የሚመስል እናጭዳለን፡- ስንዴ ዘርተን በምንም መንገድ ገብስ አናጭድም፡፡ ስንዴ የዘራ የሚያጭደው ስንዴ ነው፡፡

2.            ከዘራነው በላይ እናጭዳለን፡- ኪሎ ስንዴ የዘራ ገበሬ በዓመቱ የሚያጭደው የዘራውን ያህል አይደለም፡፡ ከዘራው በላይ ያጭዳል፡፡ ምርት የተትረፈረፈ ነው፡፡ ቃሉ፡- “ነፋስን ዘርተዋል÷ ዐውሎ ነፋስንም ያጭዳሉ” ይላል /ሆሴዕ 8÷7/፡፡

3.            ማንኛውም ዘር የአጨዳ ዘመን አለው፡- አንዳንዱ ዘር እንደ ወር ጎመን በወሩ፣ ሌላው እንደ ገብስ በ3 ወር፣ ሌላው እንደ ጤፍ በስድስት ወር ይታጨዳል፡፡ አንዳንድ ፍሬ ደግሞ በሃያ ዓመት፣ በስድሳ ዓመት ይደርሳል፡፡ መኸሩ ግን አይቀርም፡፡ አንዳንድ ሰው ሲያጠፋ በዕለት ይቀጣል፣ ሌላው ደግሞ ከሃያ ዓመት በኋላ መኸሩ ይደርስበታል፡፡
ሕይወት የመዝራትና የማጨድ ሕግ ከሆነ ሕይወት ዕድል አይደለችም፡፡ በባዶ ሒሳብ ላይ ቼክ ብንፈርም ወንጀል እንደሆነ ሁሉ እንዲሁም ያላስቀመጥነውን መልካምነት መፈለግ ወንጀል ነው፡፡ የምናጭደው የዘራነውን የሚመስል መሆኑን ማሰብ አለብን፡፡

ጌታችን እግሩ ሥር ተቀምጠው ለሚማሩት ይሟገትላቸዋል፡፡ በሌሎች ዘንድ የሚታዩት ሥራን የሚሸሹ፣ ሥራ ፈት ተደርገው ነው፡፡ ማርታ ስለ እህቷ ስለ ማርያም ያለችው ይህን ነው፡፡ ጌታ ግን የሰጠው ምላሽ፡- “ማርያምም መልካም ዕድልን መርጣለች ከእርስዋም አይወሰድባትም” የሚል ነው /ሉቃ. 10÷42/፡፡ በዚህ ምላሽ ውስጥ፡-

1.             የእግዚአብሔርን ነገር ወደን ካልጣልነው ማንም ሊወስድብን አይችልም፡፡ ሊቁ ዮሐንስ አፈ ወርቅ፡- “ሰዎች ስምህን ሊያጠፉ ይችሉ ይሆናል፣ የራስህን ጠባይ የምታጠፋው ግን አንተ ብቻ ነህ” ብሏል፡፡ ጌታም የማይሰርቁብን መክሊታችን መሆኑን አባቶች ገልጠዋል፡፡
2.            መልካም ዕድል የምንመርጠው ነው፡፡ “መልካም ዕድል ፈልጐን የሚመጣ ሳይሆን የምንመርጠው ነው፡፡

ሕይወት ዕድል ሳትሆን ምርጫ ናት ብለናል፡፡ በሕይወት ውስጥ ደግሞ እግዚአብሔር የሚሰጠን መልካም የሥራ አጋጣሚ አለ፡፡ ጌታችን ይህን ሲገልጥ፡- “ቀን ሳለ የላከኝን ሥራ ላደርግ ይገባኛል፤ ማንም ሊሠራ የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች” ብሏል (ዮሐ.9÷4)፡፡ ጌታ ቀን ያለው የሥራ ጊዜን ነው፡፡ ጌታ መሥራት የሚቻልበትን ዘመን “ቀን” አለው፡፡ ያልፋል ማለት ነው፡፡ ቀን በሌሊት ይተካልና፡፡ አንድ ባለሥልጣን ፊት ሆኜ ይህን ጉዳይ አሳውቅልን አሉኝ፡፡ እኔም በእንዲህ ያለ ግንኙነት ከሹም ጋር መቀራረብ አልፈልግም፣ ወንጌሌን ያረክስብኛል አልኩኝ፡፡ የሰማሁት ድምፅ ግን፡- “መናገር በሚደመጡበት ዘመን ነው፣ አሁን እርሳቸው የሚሰሙት አንተን ነው” አሉኝ፡፡ አሳቡን ወደድኩት፡፡ አዎ መናገር በሚደመጡበት ዘመን፣ መሥራት በሚቻልበት ጊዜ ነው፡፡ ጆሮ የምንነፈግበት ዘመን ይመጣል፡፡

ለፊልድልፍያ ቤተ ክርስቲያን ከተላለፈ የተስፋ ቃል አንዱ፡- “እነሆ በአንተ ፊት የተከፈተ በር ሰጥቼአለሁ ማንም ሊዘጋው አይችልም” የሚል ነው (ራእ. 3÷8)፡፡ የተከፈተ በር የሥራ ዘመን፣ የምንማርከው ትውልድ ነው፡፡

አንድ በንጉሡ ዘመን የተጻፈ መጽሐፍ ላይ ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ፎቶ ሥር፡-
“አገሬ ኢትዮጵያ ጠንክረሽ ተማሪ
ሁልጊዜ አይገኙም ዕድልና መሪ” ይላል፡፡

ሁለቱ ገጥመው አይገኙም፡፡ ሁለቱ ከገጠሙ ብዙ ታላላቅ ሥራ ይሠራል፡፡

እግዚአብሔር በሕይወት ላይ ልዩ አጋጣሚዎችን ይሰጣል፡፡ እነርሱም፡-
1.             ንስሐ
2.            ትምህርት
3.            የሚመክሩን ሰዎች
4.            የዕረፍት ጊዜ

1-     ንስሐ- እግዚአብሔር በግብፅ ላይ ዐሥር መቅሰፍት ያወረደው ኃይሉን በመግለጥ ከፈርዖን ጋር ለመወዳደር አልነበረም፡፡ ለፈርዖንና ለግብፃውያን የንስሐ ዕድል እየሰጠ ነበር፡፡ እግዚአብሔር የንስሐ ዕድል (መልካም አጋጣሚ) ይሰጣል፡፡ እርሱ ማንም ይጠፋ ዘንድ ፈቃዱ አይደለምና፡፡ ንስሐ ዕድል ከሆነ ይወሰዳል፡፡ ብዙ ሰዎች ንስሓን በማንኛውም ጊዜ ሊያደርጉት የሚችሉት ነገር አድርገው ይመለከቱታል፡፡ ንስሓ ግን ዕድል ነውና ይወሰዳል፡፡ ንስሓ የምንገባው የንስሓ መንፈስ ሲሰጠን ነው፡፡ እግዚአብሔር የንስሓ ድምፅ ሲያመጣ መንፈሱንም አብሮ ይልካል፡፡ ሰውዬው ወዲያው ታዝዞ ንስሓ ቢገባ መንፈሱ ያግዘዋል፡፡ ነገር ግን ከዘገየ መንፈሱ ይሄዳል ትእዛዙ ይቀራል፡፡ ደጋግመን የንስሓን ድምፅ ከገፋን በመጨረሻ እግዚአብሔር እንደ ፈርዖን ልባችንን በማጽናት ለቅጣት ያመቻቸናል፡፡

2-    ትምህርት፡- ስለ ትምህርት በተነሣ ቁጥር “የትምህርት ዕድል” የሚል ቃል አብሮ ይጠቀሳል፡፡ ትምህርት ዕድል ነው፡ እግዚአብሔር መንፈሳዊ መምህራንን ሲሰጠን ቃሉ እንደ ካፊያ ሲወርድ ይህ ትልቅ ዕድል ነውና መጠቀም ይገባናል፡፡ አሊያ ካልተጠቀምንበት ይወሰዳል፡፡

3-    የሚመክሩን፡- ምክር በብዙ ገንዘብ በሚሸጥበት ዘመን ላይ ያውም የሕይወት ምክር የሚመክሩን እግዚአብሔር የሰጠን ልዩ አጋጣሚ ነውና፡፡ ልንጠቀምባቸው ይገባናል፡፡ በአፍሪካ ውስጥ የአንድ ሽማግሌ ሞት የትልቅ ቤተ መጻሕፍት መቃጠል ነው እንደሚባለው በትምህርት ቤት የማይገኙ በጐ ዕውቀቶች የሚሰጡንን መምህራን ማክበርና መጠየቅ ይገባናል፡፡
4-   የዕረፍት ጊዜ፡- ብዙ ጊዜ ከ21 -30 ባለው ዕድሜ እግዚአብሔር የዕረፍት ዘመን ይሰጣል፡፡ ወጣቶች ትምህርት ጨርሰው ያለ ሥራ ያለ ወዳጅ የሚሆኑበት ጭው ያለ ጊዜ ይገጥማቸዋል፡፡ ጉዳዩ ምን እንደሆነ አይረዱም፡፡ ቀጣዩ ጉዞ ፌርማታው ረጅም የሆነ በረራ ነውና እግዚአብሔር የማንበብያና የጽሞና ጊዜ እየሰጣቸው እንደሆነ ስለማይረዱ በጭንቀት ያልፋሉ፡፡ የጽሞና ጊዜ ማጣት ከባድ ነው፡፡ እግዚአብሔር የሚነግረንን ምክር ተቀብለን ይህን የጽሞና ጊዜ ካላበጀን በስደት፣ በበሽታ፣ በእስር ቤት በመክተት ብቻችንን ያገኘናል፡፡

የእስራኤል ልጆች ከተሰጣቸው ትእዛዝ አንዱ ስድስት ዓመት ሠርተው በሰባተኛው ዓመት ማረፍ፣ ለምድሪቱ ሰንበት መስጠት ነው፡፡ እነርሱ ግን ይህን ትእዛዝ መጠበቅ አቅቷቸው በስስት ለ490 ዓመታት ያህል ባዘኑ ምድሪቱንም አላሳረፏትም፣ በስድስተኛው ዓመት በረከት ሰባተኛውን ዓመት የሚያኖረውን ጌታ ማየት አልቻሉም፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር የባቢሎንን ምርኮ አመጣ፡፡ የባቢሎን ምርኰ 70 ዓመት ነው፡፡ የ490 ዓመታት ሰንበት 70 ዓመት ይሞላዋል፡፡ ቃሉ፡- “በኤርምያስ አፍ የተነገረው የእግዚአብሔር ቃል እንዲፈጸም ምድሪቱ ሰንበትን በማድረግዋ እስክታርፍ ድረስ፣ በተፈታችበትም ዘመን ሁሉ ሰባ ዓመት እስኪፈጸም ድረስ ሰንበትን አገኘች” ይላል (2ዜና 36÷21)፡፡

በሕይወታችን ማረፍ አቅቶን እኔ ስቆይ ሁሉም ነገር ይቆማል በሚል አሳብ እንቅበዘበዛለን፡፡ ምናልባት ዛሬ በእስር፣ በስደት፣ በበሽታ የምናልፈው የኖርነውና የምንኖረው በራሳችን ሳይሆን በእግዚአብሔር መሆኑን እንድናስተውል ነው፡፡ ደግሞም እግዚአብሔር ብቻችንን ሊያገኘን ስለወደደ ነው፡፡ ወዳጅ የብቻ ጊዜ ይፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር ወዳጃችን ነውና የብቻ ጊዜ ይፈልጋል፡፡ በፍቅር ሲጠይቁን እምቢ ካልን ቆም አድርጎ ጊዜውን ይወስዳል፡፡

እንግዲህ ተፈጥሮ ለእኛ እንጂ እኛ ለተፈጥሮ አልተበጀንም፡፡ እግዚአብሔር የእኛና የተፈጥሮ አዛዥ ነው፡፡ እግዚአብሔርን ስንታዘዝ ተፈጥሮ ይገዛልናል፡፡ ተፈጥሮ የምንለው ቀንና ታሪክን የሚጨምር ነው፡፡ ቀኑም ታሪኩም የእኛ እንዲሆን እግዚአብሔርን መያዝ ያስፈልገናል፡፡ ይልቁንም መንፈሳዊ ነገር ምርጫ እንጂ ዕድል ባለመሆኑ ጠንክረን ልንይዘው ይገባል፡፡

በርግጥ ብዙ ሰነፎች በሀብት ሲጥለቀለቁ ብዙ አረጥራጪዎች የከበረ ነገር ሲያገኙ እናያለን፡፡ አዎ እግዚአብሔር መሥራትም መማርም የሚቸገሩትን ይረዳቸዋል፡፡ ጐበዙ በጉልበቱ ሲቆም እግዚአብሔር ደግሞ ደካማውን ያግዛል፡፡ ዕድል የምንለው ብዙ ጊዜ ገንዘብን በመሆኑ ወይም ምድራዊ ነገር ብቻ በመሆኑ አስተሳሰባችን የወረደ ነው፡፡ ይህ ዓለም የተበጀው ለመንፈሳዊ ዓላማ ነው፡፡ ስለዚህ መንፈሳዊውን ነገር አክብረንና አልቀን መያዝ ይኖርብናል፡፡ እግዚአብሔር ይህን ዓለም ከመፍጠሩ በፊት ያየው የከተሞችን ዕድገት ሳይሆን የቅድስና ኑሮአችንን ነው፡፡ እግዚአብሔር ያየልንን ስንኖር ቤታችን መሠራት ይጀምራል፡፡ ቤትን ጥረትና ምኞት ብቻ አይገነባውም፡፡ ቤተ ሠሪ እግዚአብሔር ነው፡፡ ስለዚህ ጌታዬ ሆይ እኔ ላንተ ቤት፣ አንተ ለእኔ ቤት ሥራ ልንል ይገባናል፡፡ ሕይወት ምርጫ ናትና አሁን እንምረጥ!   

2014 ኦገስት 21, ሐሙስ

“አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፥ አንተና የመቅደስህ ታቦት” /መዝ.131፥8/

“አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፥ አንተና የመቅደስህ ታቦት” /መዝ.131፥8/


Emebetachin-Erigetሰላም ለፍልሰተ ሥጋኪ መካነ ፍሥሐ ምጡቀ ፤ በአእባነ ባህርይ ዘተነድቀ ፤ማርያም ደብተራ እንተ ኢትትከደኒሠቀ፤እመቤቴ ማርያም ሆይ ምጡቅና ሩቅ ወደሚሆን የደስታ ቦታ ላረገ ሥጋሽ ሰላምታ ይገባል ፡፡ ይኸውም ኅብሩ ሊመረምሩት በማይቻል ዕንቊ የታነፀ ሕንፃ ይገኝበታል፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አዳም አባታችን እግዚአብሔርን በድሎ፣ ክብሩን አጥቶ፣ ሞተ ሥጋ ሞተ ነብስ ተፈርዶበት፣ ከገነት ሲባረር ፤ ምህረትና ቸርነት የባህሪው የሆነው አምላክ ይቅር ይለው፣ ወደ ቀደመ ክብሩ ይመልሰው ዘንድ ተማጽኗል፡፡ እግዚአብሔር አምላክም የአዳምን ማዘን፣ መጸጸት ፣ ንስሀ መግባት ተመልክቶ 5500 ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ ስደትህን በስደቴ፣ ሞትህን በሞቴ አጥፍቼ የቀደመ ክብርህን መልሼ ያጣኸውን ርስት ገነት መንግስተ ሰማያት አወርስሃለሁ፡፡ገላ4፡4 በማለት ቃል ኪዳን ገብቶለታል፡፡

አዳም አባታችን ቃል ኪዳን በተገባለት መሠረት የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ ለእግዚአብሔር ወልድ ማደሪያነት የተመረጠች፣ ለአዳም እና ዘሩ መዳን ምክንያት የሆነች የልጅ ልጅ የተባለችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዳ 15 ዓመት ሲሆናት በቅዱስ ገብርኤል ብስራት የእግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ማደሪያ ሆነች፡፡ ልጇን በወለደች ወቅት የሰብዓ ሰገልን “የተወለደው የአይሁድ ንጉስ ወዴት አለ” የሚለውን ዜና የሰማ ሄሮድስ የተወለደውን ህጻን ለመግደል አዋጅ አወጀ ፡፡ እመቤታችንም ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስን ለማዳን ወደ ግብጽ ይዛው ተሰደደች ማቴ.2፡12፡፡

የስደት ዘመኑ አልቆ ወደ ኢየሩሳሌም ከተመለሱ በኋላ ኢየሱስ ክርስቶስ 30 ዘመን ሲሆነው ስለመንግስተ እግዚአብሔር ስለ ሰው ልጆች ነጻነት ይሰብክ ጀመር፡፡ ኃላም የአዳም ዘር ሞት ለማጥፋት ፣ባርነትን አጥፍቶ ነጻነትን ለማወጅ በመስቀል ተሰቅሎ ሞተ ፡፡ በሦስተኛው ቀን ተነስቶ ነጻነትን አወጀ፡፡ በዚህ ሁሉ የድኅነት ጉዞ ውስጥ ያልተለየችና ምክንያተ ድኂን የሆነችው እመቤታችን የሰው ልጆች ድኅነት ሲረጋገጥ በተወለደች በ64 ዓመቷ ጥር 21 ቀን አረፈች፡፡

a ergete mariam 2006 1ሐዋርያት መጽናኛቸው እናታቸው ቅድስት ድንግል ማርያም ብታርፍባቸው ሥጋዋን ባጎበር አድርገው ወደ ጌቴ ሴማኒ ይዘዋት ሄዱ አይሁድ “ቀድሞ ልጇን ሰቅለን ብንገድለው ደቀ መዛሙርቱ ተነሣ፣ ዐረገ” እያሉ ሲያውኩን ኖሩ፤ ዛሬ ደግሞ እርሷን ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሊያውኩን አይደለምን? በእሳት እናቃጥላታለን” ብለው ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ተራምዶ አጎበሩን ጨበጠው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል የታውፋንያን ሁለት እጁን በሰይፍ መትቶ ቀጣው፡፡ በዚህም የታውፋንያ ሁለት እጁ ከአጎበሩ ተንጠልጥሎ ቀረ፡፡

ከዚያ በኋላ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌላዊውን ቅዱስ ዮሐንስ ጨምሮ በደመና ነጥቆ ከገነት በዕፀ ሕይወት ሥር አኖራት፡፡ዮሐንስ ከገነት ሲመለስ ለሐዋርያት “ የእመቤታችንን ሥጋ ወደ ገነት መወሰድ ነገራቸው፡፡ “ዮሐንስ የእመቤታችንን ሥጋ ገነት ማረፍ አይቶ እኛ ሳናይ” ብለው፤ ከነሐሴ 1 ቀን - ነሐሴ 14 ቀን ጾመዋል፡፡ "ሰላም ለፍልሰተ ሥጋኪ መካነ ፍሥሓ ወኑዛዜ፡ ኀበ ኢይሬእይዎ ለላህ ወኢይሔይልዎ ለትካዜ፡ ማርያም ህሉት ዉስተ ልበ ኣምላክ እምቅድመ ግዜ፡ ትፍሥሕትሰ ተፈሣሕኩ ብፍልሰትኪ ይእዜ፣ ገጸ ዚኣኪ እሬኢ ማዕዜ”ይላል መልክዓ ፍልሰታ፡፡

እግዚአብሔር ሀዘናቸውን ተመልክቶ መጽናናትን ይሰጣቸው ዘንድ ከነሐሴ 1 ቀን -ነሐሴ 14 ቀን ሐዋርያት በአንድ ልብ ሆነው ሱባኤ ያዙ (በጾም በጸሎት ተወስነው ) እግዚአብሔርም የልብ መሻታቸውን አይቶ ነሐሴ 14 ቀን ጌታ የእመቤታችንን ሥጋ ታወጣ ዘንድ ምድርን እንዲጠሩዋት ሰባቱን የመላእክት አለቆች አዘዛቸው፡፡ እነርሱም ትወጪ ዘንድ እግዚአብሔር አዞሻል አሏት፡፡ ያን ጊዜም ከዕፅ ሕይወት በታች ካለ መቃብር የእመቤታችን የማርያም ሥጋዋ ወጣ፡፡ ሐዋርያት ገንዘው በክብር ቀብረዋታል፡፡ ስለ ግንዘቷም "ሰላም ለግንዘተ ሥጋኪ ብእደ ሓዋርያት ኣርጋብ፤ ብአፈወ ዕፍረት ቅዱው ዘሐሳብ ሴቱ ዕጹብ፤ ማርያም ድንግል ውለተ ህሩያን ሕዝብ፤ ረሰይኩኪ እግዝእትየ ህየንተ እም ወኣብ፤ ይኅጽነኒ ከመ ጥብ ፍቅርኪ ሓሊብ።” ያለው ለዚህ ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድ በዝማሬ ድርሰቱ “በስብሐት ውስተ ሰማያት መላእክት ወሊቃነ መላእክት ወረዱ ለተቀብሎታ፣ እብለኪ ወእሙ ለእግዚእየ እብለኪ ዳዊት አቡሃ ምስለ መሰንቆሁ ሙሴኒ እንዘ ይፀውር ኤፉደ መጽኡ ሃቤሃ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ሐዋርያት አጠኑ ሥጋሃ በማዕጠንተ ወርቅ፣ ሱራፌል ወኪሩቤል ሰፍሑ ከነፊሆሙ ላዕሌሃ፣ ወረደ ብርሃን እምሰማያት ወመብረቀ ስብሐት እምውስተ ደመናት፣ ተለዓለት እምድር ውስተ አርያም በስብሐት ወበህየ ነበረት ዘምስለ ወልዳ በየማነ አብ ወመንፈስ ቅዱስ” ብሏል፡፡

ጌታችንም ዘላለማዊ ወደሆነ መንግሥተ ሰማያት መላእክት እና ሰማዕታት እየሰገዱላት አሳረጓት፡፡ ንጉሥ ዳዊት “በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋ ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” እንዳለ /መዝ 44¸9/፡፡ ወንጌላዊ ዮሐንስም ከእርሷ በረከትን ተቀብሎ ተመልሶ ከሰማይ ወረደ፡፡ ሐዋርያት ተሰብስበው ስለ እመቤታችን ሥጋ ፈጽሞ ሲያዝኑና ሲተክዙ አገኛቸው፡፡ እርሱም እንዳየ እንደሰማ ሥጋዋም በታላቅ ክብር ማረጉን ነገራቸው፡፡

መላእክትና ሊቃነ መላእክት ቅዱስ ሥጋዋን ለማሳረግ በታላቅ ምሥጋና ከሰማይ ወረዱ፤ አባቷ ዳዊት ከመሰንቆው ጋር ሙሴም የአገልግሎት ልብሱን ለብሶ፣ ሐዋርያት ጴጥሮስና ጳውሎስም ወደ እርሷ መጡ ሥጋዋንም በወርቅ ማዕጠንት አጠኑ፡፡ ሱራፌልና ኪሩቤልም በላይዋ ክንፎቻቸውን ዘረጉ /ጋረዱ/፡፡ ከሰማያት ብርሃን የምስጋና መብረቅም ከደመናት ውስጥ ወጣ፡፡ ከምድር ወደ ሰማያት በምስጋና ከፍ ከፍ አለች ከልጇ ጋርም በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች” ማለት ነው፡፡ ይህም “በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች፡፡” መዝ.44፥9 ተብሎ የተነገረላትን ቃለ ትንቢት የተፈጸመላት መሆኑን ያመለክታል፡፡

ከሐዋርያት ወገን የሆነው ቅዱስ ቶማስ ለወንጌል አገልግሎት ሄዶ በወቅቱ አልነበረም፡፡ ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ ሕንድ ሲመጣ ስታርግ አገኛት፡፡ “ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ” ይላል፤ ተበሳጨ፡፡ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁኝ” አለ፡፡ በዚህ ጊዜ የልቡናን ሐዘን የምታቀል እመቤታችን፡- አይዞህ አትዘን እኒያ ትንሣኤዬን ዕርገቴን አላዩም፡፡ አንተ አይተሃል፡፡ ተነሣች፣ ዐረገች ብለህ ንገራቸው፡፡” ብላ የያዘችውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው፡፡

ከዚህ በኋላ ሄዶ፤ “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው “ሥጋዋን አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ እርሱም “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር ተዉ ይህ ነገር አይመስለኝም” አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ እንጂ ልማድህ ነው፡፡ አንተ ብቻ ተጠራጥረህ አትቀርም፤ አንተ እየተጠራጠርህ ሰውን ሁሉ ስታጠራጥር ትኖራለህ” አለው፡፡ እርሱም የያዘውን ያውቃልና ጸጥ ብሎ ይሰማቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ተቆጥቶ ሂዶ መቃብሩን ቢከፍተው የእመቤታችን ሥጋዋን አጥቷል፡፡ በዚህም ምክንያት ደንግጦ ቆመ፡፡ ይህን ጊዜ ቅዱስ ቶማስ “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሣች ዐረገች” አላቸው፡፡

a ergete mariam 2006 2ቅዱስ ቶማስ የያዘውንም ሰበን እያሳያቸው፡- “ቅዱስ ሥጋዋን የገነዛችሁበት ጨርቅ /ሰበን/ ይህ አይደለምን” ብሎ ሰበኑን ሰጣቸው፡፡ ይህንንም ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ከዚህ በኋላ በዓመቱ “ቶማስ ትንሣኤሽን ዕርገትሽን አይቶ እኛ ሳናይ በማለት ጾም ጀመሩ፡፡

በ16ኛው ቀን አምልካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾ እመቤታችንን መንበር ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቅ ቄስ፣ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ራሱ ቀድሶ አቁርቧቸዋል፡፡ሐዋርያት ከዚህ በኋላ ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን በብቃት ለመወጣት ቻሉ፡፡ ይህንን ዐቢይ ምሥጢር አስመልክቶ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ተንሥአ እግዚኦ” ውስተ ዕረፍትከ፡፡ አንተ ወታቦተ መቅደስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦት” /መዝ.131፡8/፡፡

“ወትቀውም ንግሥት በየማንከ በአልባሰ ወርቅ ዑጽፍት ወኁብርት፤ በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” /መዝ.44፡9/ ሲል በ ቅዱስ ዳዊት የተናገረው ቃለ ትንቢት በንጽሐ ሥጋ፣ በንጽሐ ነፍስ፣ በንጽሐ ልቡና የጸናች የቅድስት ድንግል እመቤታችንን ዕረፍትና ትንሣኤ እንዲሁም ፍለሰት /ዕርገት/ በምሥጢር ከማሳየቱም ሌላ ወላዲተ አምላክ በልጇ በወዳጇ በኢየሱስ ክርስቶስ መንግሥት በክብርመኖሯንም ያስረዳል /ራእ.11፡19/፡፡

2014 ኦገስት 8, ዓርብ

ፆመ ፍልሰታ እና በረከቱ በቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው


የቅዳሜ ውዳሴ ማርያም ትርጓሜ

የቅዳሜ ውዳሴ ማርያም ትርጓሜ

በገ/እግዚአብሔር ኪደ
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ ነሐሴ ቀን ፳፻ ዓ.ም.)፡- በዚህም ቀን እመቤታችን ትመጣለች፤ የብርሃን ድባብ ይዘረጋል፤ የብርሃን ዙፋን ይነጠፋል፡፡ ከዚያ ላይ ኹናም ሊቁን ባርካው ምስጋናዉን ጀምሯል፡፡
፩. ንጽሕት ነሽ፤ ብርህት ነሽ፡፡ በአፍአ በውስጥ ንጽሕት ነሽ፡፡ ሊቁ “ዲያተሳሮን” በተባለው የወንጌል ትርጓሜ መጽሐፉ የእመቤታችንን ንጽሕና ሲናገር፡- “የማርያም ሰውነት የምድር ላይ መቅደስ ነው፡፡ በዚሁ መቅደስም ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላከ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በኀጢአት፣ በሞትና በርግማን ፈንታ የበረከትን ዘር ሊዘራ መጣ፡፡ የኤልሳቤጥም ሰላምታ ይህንን አረጋገጠ፡፡… አንተና እናትህ ብቻ በማንኛውም ረገድ ንጹሐን ናችሁ፡፡ ጌታ ሆይ! በአንተ ውስጥ ምንም ነቅዕ የለም፤ በእናትህም ውስጥ ምንም ምልክት የለም” ብሏል /St. Ephrem the Syrian, Commentary on Tatian’s Diatesaron, pp 91-92/፡፡

 ጌታን በማኽል እጅሽ የያዝሽው ሆይ! ምልዕተ ክብር ሆይ! (ተፈስሒ) ደስ ይበልሽእያሉ ፍጥረት ኹሉ ከአንቺ ጋር ደስ ይላቸዋል፡፡ እግዚአብሔር ከሥጋሽ ሥጋ ከነፍስሽ ነፍስ ነሥቶ ከአንቺ ጋር አንድ ባሕርይ ቢኾን ባለሟልነትን አግኝተሻልና (ተፈስሒ) ደስ ይበልሽ፡፡ ግርምት ድንግል ሆይ! ክብርሽን ገናንነትሽን ዕፁብ ዕፁብ እያልን እናመሰግናለን (እናደንቃለን)፡፡ ከማኅፀንሽ ፍሬ የባሕርያችን ድኅነት ተገኝቷልና ከመልአኩ ጋር እንደ መልአኩ ምስጋና እናቀርባለን፡፡ የማኅፀንሽ ፍሬ ከአባቱ ጋር አስታርቆናልና እንደ መልአኩ ምስጋና እናቀርብልሻለን፡፡ ሊቁ ቅድም በጠቀስነው መጽሐፉ፡- “… መልአኩ ወደ አንዲት ድንግል ተላከ፡፡ ወደ እርሷ ገብቶም “እነሆ ድንግልናሽ ሳይነዋወጽ ትፀንሻለሽ፤ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፤ ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ” አላት/ሉቃ.፩፡፴፩//፡፡ ይኸውም በሥጋ ተገልጦ ሊመጣ ስላለው ስለ አካላዊ ቃል ሲናገር ነው፡፡ ሲነግራት “ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ” አላት እንጂ “ኢየሱስ የተባለው” እንዳላላት ልብ በሉ፡፡ ይኸውም የሰው ልጆች ወልደ እግዚአብሔር በለበሰው ሥጋ የሚድኑበት ስም መኾኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ምክንያቱም ኢየሱስ ማለት በዕብራይስጥ “መድኅን” ማለት ነውና፡፡ መልአኩ “ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ” ሲላት መድኅን ትዪዋለሽ ማለቱ ነው፡፡ ለምን? ሕዝቡን ኹሉ ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና” ብሏል /ማቴ.፩፡፳፩/፡፡ ከአባቱ ጋር ካስታረቀን ልጅሽ ፅንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፪. አባ ሕርያቆስ፡- “እግዚአብሔር አብ በሰማይ ኾኖ ምሥራቅንና ምዕራብን ሰሜንና ደቡብን ዳርቻዎችንም ኹሉ በእውነት ተመለከተ፤ እንደ አንቺ ያለ አላገኘም፡፡ የአንቺን መዓዛ ወደደ፤ የሚወደው ልጁንም ወደ አንቺ ሰደደ” እንዲል /ቅዳ.ማር. ቁ.፳፬/ እንደ ሰርግ ቤት አደፍ ጉድፍ የሌለብሽ ኾነሽ ቢያገኝሽ መንፈስ ቅዱስ አድሮብሻልና፤ ኃይለ ልዑል ወልድም ሥጋሽን ለብሷልና አንድም መንፈስ ቅዱስ ከሦስቱ ግብራት ከልክሎሻልና ኃይለ ልዑል ወልድም ከሦስቱ ግብራት ከልሎሻልና ለዘለዓለሙ ጸንቶ የሚኖር አካላዊ ቃልን ወለድሽልን /ሃይ.አበ.፻፲፡፳፱/፡፡ ሰው ኾኖ ከኃጢአት አዳነን /ማቴ.፩፡፳፩/፡፡ ሰው ኾኖ ከኃጢአታችን ፍዳ ካዳነን ልጅሽ ፅንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፫. መድኃኒታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በሥጋ ወልደሽልናልና ከዳዊት ሥር የተገኘሽ ባሕርይ አንቺ ነሽ /ሉቃ.፩፡፴፪/፡፡ ቅድመ ዓለም የነበረ፣ ከአብ ባሕርይ ዘእም ባሕርይ አካል ዘእም አካል የተወለደ፣ ተቀዳሚ ተከታይ (ታላቅም ታናሽም) የሌለው አካላዊ ቃል ባሕርዩን በሥጋ ሠወረ፡፡ ከአንቺም አርአያ ገብርን ነሣ /ፊል.፪፡፯/፡፡
 ከእናንተ መካከል፡- “አካላዊ ቃል አርአያ ገብርን ነሥቶ (የባሪያን መልክ ይዞ)በሰውም ምሳሌ ኾኖ ራሱን ባዶ አደረገ ሲል ምን ማለት ነው?” ብሎ የሚጠይቅ ሊኖር ይችላል፡፡ እኛም እንዲህ ብለን እንመልስለታለን፡- ራሱን ባዶ አደረገ ሲል የእኛን ባሕርይ ገንዘብ ባደረገ ጊዜ ባሕርየ መለኮቱ ተለውጧል ማለት አይደለም፡፡ ባሕርየ መለኮቱን ትቶ መጣ ማለትም አይደለም፤ በፈቃዱ ደካማ ባሕርያችንን ገንዘብ አደረገ ማለት ነው እንጂ፡፡ ወልደ እግዚአብሔር ራሱን ባዶ ያደረገው በመቅድመ ወንጌል “ከጥንት ዠምሮ በባሕርያችን እስኪሠለጥን ድረስ ሰይጣን በተንኰል በሥጋ ከይሲ እንደተሠወረ፤ እኛም ከፍዳ መዳናችን ቃለ እግዚአብሔር በባሕርያችን በመሠወሩ ኾነ” ተብሎ እንደተጻፈ የእኛን ባዶነት በጸጋው ለመሙላት ነው፡፡ ሰው የኾነው እኛን አማልክት ዘበጸጋ ያደርገን ዘንድ ነው፡፡” የባሪያውንመልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ኾኖ ስለ እኛ ብሎ ራሱን ባዶ ካደረገ ልጅሽ ፅንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፬. አደፍ ጉድፍ ሳይኖርብሽ አምልክን የወለድሽው እመቤታችን ሆይ! በኃጢአት ብርድ የተያዘውን ዓለም ኃጢአቱን ያርቅለት ዘንድ ፀሐየ ጽድቅ ጌታ ከአንቺ ተወልዷልና፤ ነቢያት ይወርዳል ይወለዳል ብለው እንደተናገሩም ዘር ምክንያት ሳይኾንሽ፣ መለወጥ ሳያገኝሽ ወልደሸዋልና ከምድር በላይ ያለሽ ኹለተኛ ሰማይ አንቺ ነሽ፡፡ ኢትዮጲያዊው ቄርሎስም፡- “ኦ ሰማይ ዳግሚት ዘወለደቶ ለፀሐየ ጽድቅ ዘውእቱ ብርሃነ ቅዱሳን ዘሰደዶ ለጽልመት - ጨለማን ያሳደደውን (ያስወገደውን) የቅዱሳን ብርሃን የሚኾን አማናዊ ፀሐይን የወለደች ኹለተኛይቱ ሰማይ ሆይ! …” እያለ ያወድሳታል /አርጋኖን ዘረቡዕ/፡፡ ዘር ምክንያት ሳይኾንሽ ከወለድሽው ልጅሽ ፅንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፭. ከተለዩ የተለየሽ፣ ከከበሩ የከበርሽ በውስጧም ሕግ የተጻፈበት ኪዳን ያለብሽ የተሠወረ መና ያለበት መሶበ ወርቅ ያለብሽ ደብተራ (ድንኳን) አንቺ ነሽ /ዘጸ.፳፮፡፩-፴/፡፡ ይኸውም መና የተባለው ሰው ኾኖ በማኅፀንሽ ያደረው ወልደ እግዚአብሔር ነው፡፡ መተርጕማኑ ይህን የበለጠ ሲያብራሩት፡- “ድንኳኗ የእመቤታችን ምሳሌ፤ ቅድስት የነፍሷ፤ ቅዱሳን የሥጋዋ፤ ታቦቱ የመንፈስ ቅዱስ፤ ጽላት የልቡናዋ፤ ቃሉ በመንፈስ ቅዱስ የተገለጸላት ምሥጢር ምሳሌ ነው፡፡ አንድም ቅዱሳን የሥጋዋና የነፍሷ፤ ቅድስት የልቡናዋ፤ ታቦት የማኅፀኗ፤ ጽላት የትስብእት፤ ቃሉም የመለኮት ምሳሌ ነው” ይላሉ /ውዳሴ ማርያም ንባቡና ትርጓሜው፣ ገጽ ፻፸፬/፡፡ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም በአርጋኖን ዘሐሙስ ላይ፡- “ተፈሥሒ ኦ ደብተራ ብርሃን ማኅደሩ ለዐቢይ ሊቀ ካህናት - የታላቁ ሊቀ ካህናት ማደርያ የብርሃን ድንኳን ሆይ! ደስ ይበልሽ” በማለት የሊቀ ካህናት የባሕርይ አምላክ የክርስቶስ እናት አማናዊት ድንኳን መኾኗን አስተምሯል፡፡  
 አካላዊ ቃል ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ ሰው ኾነ፡፡ የክብር ባለቤት እርሱን በዚህ ዓለም ወለደችው፡፡ ለዘለዓለሙ ጸንቶ የሚኖር አካላዊ ቃል ሰው ኾኖ ከኃጢአታችን ፍዳ አድኖናልና ሰው ኾኖ ያዳነን የነባቢ በግዕ (የሚናገር በግ የክርስቶስ) እናቱ ደስ ይላታል /ዮሐ.፩፡፳፱/፡፡ ለዘለዓለሙ ጸንቶ የሚኖር አካላዊ ቃል ሰው ኾኖ ከኃጢአታችን ፍዳ ካዳነን ልጅሽ ፅንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፮. እርሱን ከወለድሽ በኋላ ማኅተመ ድንግልናሽ ሳይለወጥ ኑረሻልና የክርስቶስ እናቱ ተባልሽ፡፡ ድንቅ በሚያሰኝ ተዋሕዶ አማኑኤልን ወልደሸዋልና ባለመለወጥ አጸናሽ፡፡ ታላቁ የቤተ ክርስቲያን መምህር ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ለማንም ሴት ያልተሰጠ ለድንግል ማርያም ብቻ የተሰጠ ድንግልና ከእናትነት ጋር አስተባብራ ስለ መገኘቷ ሲገልጥ “ወሰቦሂ ወለደቶ ዐቀበ ድንግልና፣ ዘእንበለ ርኩስ ከመ በፀንሳ መንክር ትኩን መራሂተ ለሃይማኖት ዐባይ - ከድንግል ተወለደ፤ በወለደችውም ጊዜ ድንግልናዋ ያለመለወጥ አጸና፡፡ ድንቅ የሚኾን ፅንሷ ለደገኛው ሃይማኖት መሪ ትኾን ዘንድ” በማለት ቅድስት ድንግል ማርያም አምላክን ስትወልድው ማኅተመ ድንግልናዋ እንዳልተለወጠ ጌታም ሰው ሲኾን ባሕርየ መለኮቱ ላለመለወጡ፣ እርሷ ድንግል ወእም (ድንግልም እናትም) ስትባል እንደምትኖር አካላዊ ቃል ክርስቶስም አምላክ ወሰብእ (ሰው የኾነ አምላክ) ሲባል የሚኖር የመኾኑን የተዋሕዶ ልዩ ምሥጢርን ያወቅንባት የተረዳንባት እርሷ ብቻ መኾኗን አስተምሯል /ሃይ.አበ.፷፮፡፴፪/፡፡ እንዲህ ካለ ልጅሽ ፅንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፯. ከምድር እስከ ሰማይ ደርሳ፣ በላይዋ ዙፋን ተነጽፎባት፣ በዚያ ላይ ንጉሥ ተቀምጦባት፣ መላእክት ሲወጡባት ሲወርዱባት ያዕቆብ በፍኖት ሎዛ ያያት የወርቅመሰላል አንቺ ነሽ /ዘፍ.፳፰፡፲-፳፪/፡፡ ሰው ከመኾኑ አስቀድሞ ሰውም ከኾነ በኋላ የማይመረመር እርሱን በተፈትሖ በማይታወቅ በማኅፀንሽ ችለሸዋልና እኛን ስለማዳን ከአንቺ ሰው ከኾነ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ሰዋስው (አማላጅ) ኾንሽን፡፡ እኛን ስለማዳን ከአንቺ ሰው ከኾነ ልጅሽ ፅንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፰. ጽርሐ ንጽሕት ሆይ! እነሆ ጌታ የፈጠረውን ዓለም ኹሉ በቸርነቱ ብዛት ያድን ዘንድ ከአንቺ ተወለደ፡፡ ቸር ሰው ወዳጅ ነውና በአፍአ በውስጥ እናመስግነው፡፡ቸር ሰው ወዳጅ ከኾነ ልጅሽ ፅንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡
፱. አደፍ ጉድፍ የሌለብሽ ድንግል ምልዕተ ክብር ሆይ! ደስ ይበልሽ፡፡ ከእናትሽ ማኅፀን ጀምሮ መንፈስ ቅዱስ ጠብቆሻልና የዓለም ኹሉ መክበሪያ ንጽሕት ጽዋዕ ነሽ (ከሥላሴ ለምንጠጣው ክብር ምክንያት አንቺ ነሽ)፡፡
 እንደ ደብተራ ኦሪቷ ማለትም ሙሴና አሮን በቀዳማይ ሰዓተ ሌሊት አብርተው በቀዳማይ ሰዓተ መዓልት እንደሚያጠፏት ፋና ያይደለሽ የማትጠፊ ፋና ነሽ /ዘጸ.፳፭፡፴፩-፵/፡፡
 እንደ ቀደመችው የኦሪት ቤተ መቅደስ ያይደለሽ የማትፈርሺ መቅደስ ነሽ /፩ኛ ነገ.፯፡፵፰-፶/፡፡ ሊቁ አባ ጊዮርጊሥ ዘጋሥጫም፡- “አንቲ ውእቱ መቅደስ ዘሐነጸ ሰሎሞን ወአስቀጸላ በሜላትሮን ወለበጠ ዳቤራ በውሳጥያተ መቅደስ፤ … - ሰሎሞን ያሠራት እንደ ዝናር እንደ ዐምድ ባለ ወርቅ የጠፈሯን ዙርያ ያስጌጣት፤ በመቅደስ ውስጥ ያለቺውን ቅድስተ ቅዱሳንዋን ዐውደ ምሕረቷን ግድግዳዋን በጥሩ ወርቅ ያስጌጣት፤ ቁመቱ ሃያ ክንድ፤ ክንፉ ዐሥራ አምስት ክንድ የሚኾን ኪሩብን በውስጧ ያሣለባት ቤተ መቅደስ አንቺ ነሽ” በማለት በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች እመቤታችን ሰሎሞን ባሠራት የወርቅ ቤተ መቅደስ መስሎ ኹለንተናዋ በንጽሕና በቅድስና ያጌጠች የተዋበች መኾኗን አስተምሯል /አርጋኖን ዘዐርብ/፡፡ ዳሩ ግን እመቤታችን በንጽሕናዋ በቅድስናዋ በሰሎሞን ቤተ መቅደስ ብትመሰልም ሊቁ (ኤፍሬም) እንዳለው ክብሯ የላቀ ነው፤ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ናትና የማትፈርስ መቅደስ ናት /መዝ.፹፮፡፩-፭/፡፡
 የማትለወጥ የቅዱሳን ሃይማኖታቸው (ቅዱሳን የሚያምኑበት ክርስቶስን የወለድሽላቸው አንቺ) ነሽ፡፡ ድንግል ሆይ! በውስጥ በአፍአ በነፍስ በሥጋ ይቅር ይለን ዘንድ፣ ኃጢአታችንን ያስተሠርይልን ዘንድ ከልጅሽ ዘንድ አማልጅን፡፡ኃጢአታችንን ከሚያስተሠርይልን ልጅሽ ፅንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን፡፡

አነሣሥቶ ላስጀመረን አስጀምሮ ላስፈጸመን ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይግባው አሜን!!!


2014 ኦገስት 2, ቅዳሜ

ዮሴፍ ፃድቅ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ


አምላክ አሜን!





እንኳን ለቅዱስ ዮሴፍ በዓለ እረፍት በሠላም አደረስዎት!

   
      አባቱ ያዕቆብ እናቱ ደግሞ ዮሐዳ ትባላለች፡፡ ቅዱስ ዮሴፍ   የእንጨት   ስራ   ባለሞያ  ስለነበር  ቤተሰቡን ያስተዳደር የነበረው በዚህ ስራው ነው ፡፡ በዚህም  የተነሳ ጠራቢው ዮሴፍ  በማለት  አይሁድ  ብዙ  ጊዜ  ስሙት ይጠሩት እንደነበር መፅሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡
     የአራት  ወንዶችና  የሦስት  ሴቶች  ልጆች  አባት ነው፡፡ ማቴ.13፡55 አረጋዊው  ከእመቤታችን  ከቅድስት ድንግል  ማርያም   ጋር   ያለውን   የሥጋ   ዝምድና ስንመለከት፡፡       
 አልዓዛር ማታንነናቅስራነን ወለደ ማታን ያዕቆብን ያዕቆብ ዮሴፍን ወለደ ቅስራ ደግሞ  እያቄምን እያቄም ማርያምን ወለደ፡፡
                                    
     አረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ ከ1985 አረጋዊያን  መካከል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ለማገልገል በ84 ዓመቱ ተመረጠ፡፡
የተመረጠውም በሦስት ምስክርነት ነው፡-
1.  በትሩ አብባና  አፍርታ  የእመቤታችን  ጠባቂ  እሱ እንደሆነ ተፅፎባት በመገኘቱ፡፡
2. ርግብ በተለየ ሆኔታ በአረጋዊው በቅዱስ ዮሴፍ  ላይ በማረፏ
3. ዕጣ  ቢያወጡ  ለአረጋዊው  በመውጣቱ  ምክንያት ነው፡፡
    የአምላክን    እናት    ለማገልገልና      በድንጋይ ከመወገር   እንዲጠብቃት    የተመረጠው    አባታችን ቅዱስ ዮሴፍ   በእርጅናው  ወራት   ደከመኝ   ሰለቸኝ ሳይል  አገልግሏል፣  በስደት  ጊዜ  በበርሃ  ተንከራቷል፣ አምላኩን   እንደ   አባት    አሳድጎታል   እንዲያውም  የእንጨት ስራ  በሚሰራበት  ወቅት  ስራውን  ያከናውን የነበረው ለጌታ አንድ  የራሱ  መቀመጫ  ሰርቶለት ፊት ለፊቱ  አስቀምጦት  ዓይን  ዓይኑን  እያየለው እንደነበር ገድሉ ይነግረናል፡፡
     አረጋዊው    ቅዱስ     ዮሴፍ      ከእመቤታችን  በሃዘኗም    በደስታዋው   ጊዜ     አብሯት    በመሆን አገልግሏታል፡፡
    በመፅሐፍ  ቅዱስ  ላይ  ተፅፎ  እንደምናነበው ሙሴ በፈፀመው   ስህተት    (እራሱን   ከእግዚአብሔር  ጋር    አስተካክሎ ‹‹ከዚህ   ድንጋይ     ውሃ እናወጣላችኋለን››   ዘሁ.20፡10-13  በማለቱ)    አርባ  አመት  የደከመበትን     አገልግሎት     ከነአንን     እንደማይወርሳት      እና   እንደሚሞት   ቢነገረውም አገልግሎቱን ግን ቀጠለ፡፡
    እሱ   ያገለግል    የነበረው    ስለ   እግዚአብሔር ፍቅርና  ስለ   እውነት    ነበር   እንጂ   ስለ   ከነአን አልነበረም፡፡ ልክ  እንደሙሴ   ሁሉ   በብሉይ   ኪዳን የነበሩ አባቶች ከሞት  በኋላ  ወደ  ሲዖል  እንደሚወርዱ እያወቁ   በዘመናቸው  ሁሉ እግዚአብሔርን አገልግለው አልፈዋል፡፡ 
    በሐዲስ  ኪዳንም  የመጀመሪያው  ሐዋሪያ  የሆነው አረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ   በስደት   ወቅት   ልጁ   ዮሳ ሔሮድስን ከኋላቸው ስለላከባቸው አራት ሰራዊት ጦር  እና  በቤተልሔምና   በአውራጃዋ  ስለተፈፀመው የእናቶች መከራና የህፃናቱ  ሲቃ  አንድም  ሳይቀር በነገራቸው ሰዓት  እመቤታችን    ቅድስት     ድንግል   ማርያም   በከፍተኛ   ደረጃ    በመደንገጧ     ጌታም  የእናቱን ድንጋጤ ተመልክቶ   ‹‹ዮሳ  አመጣጥህ  ዋጋ የሚያሰጥ   ነበር   ነገር  ግን  እናቴን  በማይገባ አስደነገጥካት በል በዳግም  ምፅአት  መጥቼ   ዋጋህን  እስክሰጥህ  ድረስ   ይችን    ድንጋይ   ተንተርሰህ  ለዘመናት  አንቀላፋ››  በማለት  ስለተናገረው   ዮሳ  ከዚያች   ደቂቃ   ጀምሮ  ነፍሱ ከሥጋው ተለይታው ሞተ፡፡
     አረጋዊው ቅዱስ የሴፍ  ይሔን  ሁሉ  በዓይኑ እያየ በቃ  ከዚህ  በኋላ  ልጄን ገሎብኛል  ማገልገል  የለብኝም ሳይል  እና  ሳሳይማረር   ታማኝ    አገልጋይ   መሆኑን አሳይቶናል፡፡
ዮሴፍ ፃድቅ ነበር፡፡ ማቴ.1፡19
     ጻድቅ  ማለት    እውነተኛ    ለእውነት    የቆመ ቅድስና ያለው በመልካም  ሥራው  የተመሰከረለት፣ ከክፉ ስራ  ሁሉ  የራቀ፣  በማንኛውም  ነገር  ነቀፋ የሌለበት ደግና ንፁህ ሰው ማለት ነው፡፡
     ነቢዩ  ሙሴ  በኃላፊነት   ለሚመራው  የእስራኤል ሕዝብ     የሚከተለውን     መመሪያ    ሰጥቶ    ነበር ‹‹የአምላክህን  የእግዚአብሔርን    ቃል   ብትሰማ   ዛሬ ያዘዝኩህን   ትዕዛዙን   ሁሉ    ብታደርግ    ብጠብቅም አምላክህ  እግዚአብሔር  ከምድር አሕዛብ ሁሉ ከፍ  ከፍ ያደርግሃል የአምላክህንም የእግዚአብሔርን ቃል  ብትሰማ  እነዚህ   በረከቶች   ሁሉ   ይመጡልሃል  ያገኙኅማል፡፡ አንተ በከተማህ ብሩክ ትሆናለህ …..›› ዘዳ.28፡1-7
     የአምላክን    ቃልና      ትዕዛዝ     ለመስማትና ለመጠበቅ  በረከትንም  ለማግኘት  በወቅቱ   የታደለው የእስራኤል  ሕዝብ   ነው፡፡   ዮሴፍም   ከዚህ   ሕዝብ መካከል የተገኘ እስራኤላዊ ፃድቅ ነበር፡፡
     የአረጋዊው  የቅዱስ  ዮሴፍ   ፃድቅነት   በምናኔ፣ በገዳም    በሚደረግ     ተጋድሎ     ሳይሆን   አብሮ በሚኖርበት     ሕብረተሰብ     ውስጥ     በሚያሳየው ደግነትና በነበረው ፍፁምነት ነው፡፡
     አረጋዊው  ቅዱስ  ዮሴፍ   በፈፀመው   ተጋድሎና በሳየው ታማኝነት እግዚአብሔር ለወዳጆቹ ባዘጋጀው እና  በሚሰጠው     ደስታና    ክብር    የፅድቅ    አክሊል ለመቀናጀት በ114 ዓመቱ  ሐምሌ  26   ቀን   በክብር አርፏል፡፡
‹‹የቅዱሳኑ ሞት በእግዚአብሔር ፊት  የከበረ  ነው›› መዝ.115፡6

ጸሎቱና በረከቱ በሁላችን ላይ ይደርብን አሜን!

ቅዱስ ዮሴፍ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን 

የታመነ የከበረ የተመሰገነ ስለሚሆን ስለ ዮሴፍ የምንናገረውን ዕንወቅ እርሱ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም የሚፈጸመውን ምሥጢር አላወቀምና፡፡
አገልጋይ የሆነለት ምሥጢር ምንም እንደሆነ አላወቀም ለእርሱ ከታጨችለት ከድንግል ነቢያት ስለ እርሱ የተናገሩለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ ዘር እንዲወለድ አላወቀም በነቢይ እንደተናገረ ሕፃን ያለ አባት ከድንግል እንዲገኝ አላወቀም፡፡ኢሳ 7፡14፣9፡6-7፣ ዮሐ1፡46፡፡
ከንጹሕ ዘር የተፈጠረች ድንግል የእግዚአብሔር ማደርያ እንድትሆን አላወቀም ዘለዓለም መለወጥ የሌለበት ዳግማይ አዳም ክርስቶስ ድንግልና ካላት ገነት እመቤታችን እንዲገኝ አላወቀም፡፡ዘፍ 9፡27፣መኃ 4፡12
ፍጡራንን ሁሉ የፈጠረ ክርስቶስ ያለ ዘር እንዲወለድ አላወቀም በምድራችን ታየ ተብሎ በነቢይ እንደተናገረና ዳግመኛም ምድር ፍሬን ትሰጣለች ተብሎ እንደተናገረ ፡፡ኢሳ 32፡1-2፣ዮሐ1፡4፣ቆላ 1፡15-18፣መኃ2፡12፣መዝ 85፡12
የድንግል ሆድዋ ገፋ ያለዘር የፀነሰች ድንግልን የሆድዋን መግፋት ባየ ጊዜ የዮሴፍ ልቡ አዘነ የንጽሕት እመቤታችንን ምሥጢን ፈጽሞ መረመረና በማያውቀው ምሥጢር ጸንሳ ቢያገኛት በጽኑ አሳብ በማውጣት በማውረድ ተያዘ፡፡
ፀንሳ አገኛት በዘር የፀነሰችም መሰለው ከር የሚወለደው በግብረ መንፈስ ቅዱስ ነውና አንተም እንደምትጠራጠረው አይደለምና ዮሴፍ አትፍራ ብሎ ከእግዚአብሔር የተላከ መልአክ እስኪነግረው ድረስ፡፡

ዮሴፍም ይህን በሰማ ጊዜ ለድንግል ሰገደ ንጽሕናዋንም አመነ ነቢዩ ኢሳይያስ እነሆ ድንግል ትጸንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙም አማኑኤል ይባላል ትርሜው እግዚአብሔር ከእኛ ባሕርይ ጋር አንድ ሆነ ማለት ነው ብሎ የተናገረላት ድንግል እር እንደሆነች ዐወቀ፡፡ማቴ 1፡18-25፣ሉቃ 1፡26-39፣ኢሳ 7፡14፡፡/ሃይማኖተ አበው ዘ ቅዱስ ኤራቅሊስ ምዕራፍ 48 ክፍል 8 ቁጥር 29-35 እንን ለፃዲቁ አባታችን ለቅዱስ ዮሴፍ በዓለ እረፍት በሰላም አደረሰን በረከት ረድኤቱ አይለየን አሜን፡፡