2014 ጁላይ 25, ዓርብ

መላእክትን ‹‹ያድናሉ›› ማለት ስሕተት ነውን?


ቅዱስ ዳዊት በግልጥ ‹‹የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፤ ያድናቸውማል›› ይላል፡፡ (መዝ33.7) ጥቅሱ ‹‹ያድናቸውማል›› ማለቱን ልብ በሉ፡፡ መላእክት የማያድኑ ቢሆኑ ኖሮ ቅዱስ ዳዊት በዚህ መልኩ ግልጥ አድርጎ ‹‹ያድናቸውማል›› ይል ነበር? መጽሐፍ ቅዱስ ከመሰከረው እውነት የሚበልጥ ዕውቀት አለንን? እርሱ ‹‹ያድናሉ›› እያለ እኛ ‹‹አያድኑም›› ብንል ምን ማለታችን ነው? ይህ ጥቅስ ውሸት ነውን? ይህንን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል እንታዘዘዋለን? እናምነዋለን? ወይስ ልናርመው እንወዳለን?

በሌላም የመጽሐፍ ቅዱስ ገጸ ንባብ ውስጥ ‹‹ከክፉ ነገር ሁሉ ያዳነኝ መልአክ እርሱ እነዚህን ልጆች ይባርክ›› በማለት ያዕቆብ የልጅ ልጆቹን እንደባረከ እናነባለን፡፡ (ዘፍ48.16) በዚህ ጥቅስ ውስጥ መልአክ ‹‹ከክፉ ነገር ሁሉ›› እንደሚያድን በግልጽ ተጽፏል፡፡ መላእክት ‹‹ያድናሉ›› ላለማለት እነዚህን ግልጽ ቃላት መላእክት ይጠብቃሉ፤ ይራዳሉ፤ ያግዛሉ በማለት ማድበስበስ ይኖርብን ይሆን? ይህ ሁሉ ዝርዝሩ ሥራቸው ቢሆንም እንደሚድኑም ተጽፏልና ማመን ያስፈልጋል፡፡

በዚህ መልኩ መጽሐፍ ቅዱስ በግልጥ የተናገረውን ቃል እናቶችና አባቶች በስእለታቸው ‹‹ቅዱስ ሚካኤል አድነኝ፤ ቅዱስ ግብርኤል ድረስልኝ›› እያሉ በመድገማቸው የዋሃን ስለሆኑ መጽሐፍ ቅዱስ ስለማያውቁ ነው መባል አለባቸው? ቅዱስ ዳዊትና ቅዱስ ያዕቆብ የመላእክትን አዳኝነት በግልጽ ያወጁት መጽሐፍ ቅዱስን ወደ መንፈሳዊ ኮሌጅ ገብተው ስላልተማሩ ይሆን? ወይስ አንድ ሰባኪ የመላእክትን አዳኝነት ስላስተማረ ‹‹ገድል ጠቃሽ›› በሚል መጥላላት አለበት? ዘማርያኑስ በዚህ መልኩ መዘመራቸው ሊያስወቅሳቸው ይገባ ነበር?

መላእክት የእግዚአብሔር ናቸው፡፡ የፈጠራቸው እርሱ ነው፡፡ የሚፈጽሙትም የእርሱን ፈቃድ ነው፡፡ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ የእርሱ መሆናቸውን በሚያሳይ አገላለጥ ‹‹መልአኩ፣ የጌታ መልአክ፣ መላእክቱ›› እያለ ይጠራቸዋል፡፡ ‹‹የጌታ መልአክ በሕልም ታየው›› እንዲል፡፡ (ማቴ1.20) መላእክት ሲያድኑ ፈጣሪ ሥራ አልሠራም ማለት አይደለም፡፡ መላእክት ያለ እርሱ ፈቃድ ምንም ሊያደርጉ አይችሉም፡፡ ሥራ እንዲሠሩ የሚፈቅድላቸውና የሚያዛቸው እርሱ ነው፡፡ ስለዚህ እነርሱ የሠሩትን ይዘን ‹‹ፈጣሪ ይህን አደረገ ማለት እንችላለን›› እርሱ አዟቸውና ፈቅዶላቸው እስከሠሩት ድረስ እርሱ ሠራ ማለት ነውና፡፡ የሚቀጥሉት ሦስት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምሳሌዎች ይህን ሐሳብ የሚያስረዱ ናቸው፡፡

ለምሳሌ፡- ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ጅራፍ እንዲሠሩ አዘዛቸው፡፡ ራሱ ግን ጅራፍ አልሠራም፡፡ ቢሆንም ግን መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ እንደሠራ አድርጎ ‹‹የገመድ ጅራፍ አበጅቶ›› ይላል፡፡ (ዮሐ2.15) ዳግመኛም ኢየሱስ ክርስቶስ ማንንም አላጠመቀም ሐዋርያቱ ግን እንዲያጠምቁ አዟቸዋል፡፡ ያዘዛቸው እርሱ በመሆኑ ‹‹ያጠምቃል እጅግም ደቀመዛሙርት ያደርጋል›› የሚል ወሬ በፈሪሳውያን ዘንድ ተሰምቷል፡፡ ራሱ ግን ማንንም አላጠመቀም ነበር፡፡ (ዮሐ4.1-3) ሌላ ምሳሌ ለመጨመር እነ ሐና እና ቀያፋ ራሳቸው ኢየሱስ ክርስቶስን አልሰቀሉትም፡፡ ነገር ግን ተባባሪዎችና ትእዛዝ ሰጪዎች ስለነበሩ ቅዱስ ጴጥሮሰ ‹‹እናንተ በሰቀላችሁት›› ሲል ሰቃዮች መሆናቸውን ጠቅሶ ወቅሷቸዋል፡፡ (የሐዋ4.10)

በአንጻሩ ደግሞ ሥልጣኑ የፈጣሪ ነው ማለት መላእክት ‹‹ይህን ሠሩ›› አይባልም ማለት አይደለም፡፡ ፈጣሪ በመላእክት ሲሠራ መላእክትን እንደ ቁስ ቆጥሮ ይሠራባቸዋል ማለት አይደለም፡፡ መላእክት ሕያዋን ናቸው፡፡ የማዘንና የመደሰት ስሜት አላቸው፡፡ ባይሆን ኖሮ ንስሐ በሚገባ ኃጢአተኛ ደስ እንደሚላቸው አይጻፍም ነበር፡፡ ስለዚህ መላእክት ደስ እንደሚሰኙ ሁሉ ያዝናሉ ማለት ነው፡፡ ፈጣሪ ሲያዛቸው በፈቃደኝነት ይታዘዛሉ፡፡ ፈጣሪ በእነርሱ ይሠራል ማለት ያለፈቃዳቸው ይልካቸዋል ማለት አይደለም፡፡ እንደ ሰው ልጅ ነጻነት አላቸው፡፡ ቢሆንም በእርሱ ፈቃድ ደስ ስለሚላቸው ከፈቃዱ ፈቀቅ አይሉም፡፡ ነጻ ፈቃድ ባይኖራቸው ኖሮ ሰይጣን በደለኛ ሆኖ አይገኝም ነበር፡፡ የሰይጣን ወደ ገዛ ፈቃዱ ማዘንበል ለመላእክት የተሰጣቸውን ነጻነት ያሳያል፡፡ ታዲያ ሥራቸውን ወደው የሚሠሩ ሆነው ሳለ ፈጣሪ ልኮአቸው መላእክት ቢያድኑ ‹‹አላዳኑም›› እንዴት እንላለን? ለማዳን ፈቃደኛ ሆነው እስካዳኑ ድረስ ‹‹አድነዋል፣ ያድናሉ›› ማለት የሚገባ አይደለምን?

መላእክት እግዚአብሔር ስለፈቀደላቸው የሠሩትን ሥራ እነርሱ አልሠሩትም ካልን ሰይጣን የፈጸመውን የጥፋት ተግባር ማን ሠራው ልንል ነው? መቼም እግዚአብሔር ሳይፈቅድለት ሰይጣንም ቢሆን ያሰበውን ማከናወን እንደማይችል የታወቀ ነው፡፡ ታዲያ ሰይጣን የሠራውን ፈቃጁ አካል እግዚአብሔር ስለሆነ ፈጣሪ ይህን አደረገ እንጂ ሰይጣን ይህን አልሠራውም እንላለንን? እንዲሁም ፈቃጁና አዛዡ ምንም ፈጣሪ ቢሆን ቅዱሳን መላእክት የሠሩትን እንደሠሩት ማመንና መመስከር ይገባል፡፡ ለክፉ ሥራው ሰይጣን ኃላፊነቱን እንደሚወስድ ሁሉ ቅዱሳን መላእክትም ለሥራቸው ኃላፊነቱን ይወስዳሉ፡፡ ስለዚህ ፈጣሪ ቅዱስ ገብርኤልን ልኮ ቂርቆስንና ኢየሉጣን ስላዳነ ‹‹ቅዱስ ገበርኤል አዳናቸው!›› የሚገባ ነው፡፡

በቅዱሳን መላእክት ማዳንና ተራዳኢነት ውስጥ የእግዚአብሔር ሥልጣንና አዛዥነት በረቂቅ አለበት፡፡ እግዚአብሔር ሰዎችን ለማዳን በምንም መንገድ ቢሠራ በዛ ውስጥ የእርሱ ሥልጣንና ሥራ የማይጠረጠር ነው፡፡ መላእክት ያለ ፈጣሪ ትእዛዝና ፈቃድ አንዳች ሊሠሩ አይችሉም፡፡ ፈጣሪ ግን ያለ መላእክት አጋዥነት የፈለገውን የሚሠራ ሁሉን ቻይ አምላክ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ፈጣሪ ይህን ሠራ ስንል መላእክትን ላይጨምር ይችላል፡፡ መላእክት ይህን አደረጉ ስንል ግን በምንም ተአምር ከፈጣሪ ውጭ ሊሆን አይችልም፡፡ ስለዚህ መናፍቃን ‹‹ጌታ፣ እግዚአብሔር ይህን አደረገ›› ብቻ እንድንል የሚፈልጉት ቅዱሳንን ላለማስገባት ነው፡፡ እኛ ኦርቶዶክሳዊያን ቅዱሳን መላእክትንና ቅዱሳን ሰዎችን ይህን አደረጉ የምንለው እግዚአብሔርን ከማመን ጋር ስለ ቅዱሳን ክብር ለመመስከር ነው፡፡

እሳት በባሕርይው የሚፋጅ መሆኑ ይታወቃል፡፡ እንጨትና ብረት ግን ብቻቸውን ሳሉ ቢነኳቸው አያቃጥሉም፡፡ ነገር ግን ከእሳት ጋር ከተዋሐዱ /ከጋሉ/ በኋላ ቢነኳቸው ይፋጃሉ፡፡  እሳት የተዋሐደው ብረት የማያቃጥልበት ምንም ሁኔታ የለም፡፡ ካላቃጠለ ወይ እሳት አልተዋሐደውም ወይም ደግሞ እሳቱ ራሱ አያቃጥልም ማለት ነው፡፡ እንደዚሁም እግዚአብሔር በባሕርይው አዳኝ ነው፡፡ መላእክት አያድኑም ካልን ወይ እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር አይደለም ማለት ነው ወይም ደግሞ እግዚአብሔር ራሱ አያድንም እንደማለት ይቆጠርብናል፡፡ ስለዚህ ‹‹መላእክት ያድናሉ›› ስንል የሚያድን እግዚአብሔር ከእነርሱ እንደማይለይ እየመሰከርን መሆኑን ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡


የእግዚአብሔር ቸርነት
የመልአኩ የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አይለየን!

ዲያቆን ኅብረት የሺጥላ


2014 ጁላይ 23, ረቡዕ

አንብቦተ መጽሐፍ በቅዱስ ኤፍሬም



ትርጉም በዲ/ ሽመልስ መርጊያ




           ቅዱስ ኤፍሬም ስለአንብቦተ መጽሐፍ  ፖፕሊየስ ለሚባል ወዳጁ በጻፈው ደብዳቤው ላይ እንዲህ ብሎ እናገኘዋልን፡-
ንጹሕ መስታወት የሆነውን የጌታችንን ቅዱስ ወንጌል በእጅህ መያዝን ስላልተውክ መልካምን አደረግህ ፡፡ በእርሱ መስታወትነት ማንም ምን መምሰል እንዳለበት ይረዳበታል ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስን የሚያነቡ ወገኖች በዚያ ውስጥ ምስላቸውን ከማግኘታቸው በተጨማሪ የራሳቸውን ተፈጥሮ በማስተዋል ከነውር እንዲጠበቁትና በቅድስና ጸንተው ያለመለወጥ እንዲመላለሱ ይረዳቸዋል ፡፡ በሰውነታቸውም ላይ ነውር አይገኝም ከእድፍም የጸዱ ይሆናሉ ፡፡ 
በመስታወት ፊት ባለቀለም ቁስ ቢቆም እንደቀለሙ ዓይነት እንዲሁ መስታወቱ ይሆናል ፡፡ ነገር ግን የመስታወቱ  ባሕርይው አይቀየርም ፡፡ ነጭ የሆነ ቁስ በፊቱ ቢያቆሙ ያንኑ ነጭ ቁስ መልሶ ያሳየናል ፡፡ ጥቁር ቀለም ያለው ቁስ በፊቱ ቢቆም የጥቁረቱን መጠን ያሳየዋል ፡፡ ቀይ ከሆነም ቅላቱን ያሳየዋል ፡፡ ውብ ገጽታ ካለው ደግሞ ውብቱን ያሳየዋል ፡፡ መልከጥፉም ከሆኑ እንዲሁም ለዐይን ምን ያህል እንደሚያስቀይሙ ያሳያቸዋል ፡፡ እያንዳንዱን የሰውነታችንን ገጽታ በዚህ መስታወት ውስጥ እናየዋለን ፡፡ 

መልከ ጥፉዎች በዚህም በመጽሐፍት መስታወትነት ራሳቸውን ተመልክተው ስለመልከ ጥፉነታችው ራሳቸውን ይገሥጻሉ ስለዚህም ራሳቸውን ከጉድፍ ያጸዳሉ አስቀያሚ ሆነው እንዲታዩ ያበቃቸውን ቆሻሻ ያስወግዳሉ :: ለቆነጃጅቶችም ውበታቸውን ጠብቀው እንዲዘልቁና ቆሻሻም እንዳይነካቸው እንዲጠነቀቁ እንዲሁም ተፈጥሮአዊ ውበታቸው ላይ አክለው እንደ ምርጫቸው ራሳቸውን እንዲያስውቡ ያተጋቸዋል ፡፡ 
ምንም እንኳ መጽሐፍ ቅዱስ ቃል አውጥቶ ባይናገርም በፀጥታው አብዝቶ ይጮኸል ፡፡ እርሱን ሕይወት የሌለው ግዑዝ ነገር አድርገህ ብትቆጥረውም ፤ጽድቅን ያውጃል ፡፡ የማይንቀሳቀስ ቢሆንም በደስታ ይቦርቃል ፡፡ ምንም እንኳ ሥጋን የለበሰ ባይሆን ማኅፀኑ እጅግ የከበረ በውስጡም ልዩ ልዩ እልፍኞች ያሉት ነው እያንዳንዱም የአካል ክፍል በውስጡ ይሠራል ፡፡ የእያንዳንዱ የአካል ቅርፅ ክፍልፋዮች በቅጽበት ይበጃጃሉ በእርሱ ውስጥ በማይታመን ፍጥነትም ይፈጠራሉ ፡፡
ይህ መስታወት በክርስቶስና በሐዋርያት ለሚሰበከው ወንጌል ምስል ነው ፡፡ በውስጡ በእርሱ ውበታቸውን የሚመለከቱበት መስታወት ይገኛል ፡፡ በእርሱም መልከጥፉዎች ነውራቸውን እንዲያዩ ስለሚሆኑ ስለመልከጥፉነታቸው ይገሠጻሉ ፡፡ ይህ መስታወት ልክ እንደ ተፈጥሮአዊ መስታወት ነው ፡፡ ነገር ግን የወንጌል ምስል ነው ፡፡ በሐዋርያት የተሰበከው ወንጌልም ከምስሉ(ከመጽሐፉ) ይልቅ ከላቀው ከማይጠፋው ከእርሱ የተገኘ ነው ፡፡ በእርሱ የፍጥረት መተላለፍ ሁሉ ይገሠጻል ፡፡
በእርሱም ራሳቸውን በኃጢአት ጭቃ ሳያሳድፉ ለጸኑት ክብርን ያጎናጽፋል ፡፡ በዚህ መስታወት ራሱን የሚመለከት ኃጢአቱን ይረዳል ፡፡ ይህንን የተረዳ ሰው ስለራሱ በጎነት ወይም መተላለፍ ስለሚያቅ ራሱን አስተካከሎ መምራትን ያውቃል ፡፡በዚያ ውስጥ ዐይኖቻቸው ንጹሐን የሆኑላቸው ወገኖች መንግሥተ ሰማያትት በውስጡዋ ተስላ ያገኙዋታል ፡፡ በእርሱ ውስጥ ያለው የእግዚአብሔር መልካሙ ስጦታ ጎልቶ ይታያል ፡፡ በዚያ ውስጥ መካከለኛ የተባለው የክርስቶስ ክብር ከፍታ ይታያል ፡፡ በዚህ እግዚአብሔር ለቅዱሳኖች ያዘጋጃቸው ማደሪያዎች እንዳሉ ማረጋገጥ ይቻላል ፡፡ በዚህ ውስጥም በገነት ያለው ተድላ ደስታ በግልጽ ይታያል ፡፡