2014 ጁላይ 13, እሑድ

ውዳሴ አምላክ ዘሰኑይ

ውዳሴ አምላክ ዘሰኑይ
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስቅዱስ ስም አምነን የቂሳርያ ኤጲስ ቆጶስ ባስልዮስ የደረሰውን የልመናና የምልጃ ጸሎት ያለበትን ዘወትር ሊጸልዩት የሚገባ ውዳሴ አምላክ የሚባል መጽሐፍ በእግዚአብሔር አጋዥነት እንጀምራለን የአባታችን የባስልዮስ ጸሎት ይጠብቀን ረድኤቱ አይለየን አሜን ይደረግን፡፡
አምላኬ ሆይ ሠውሬ የሠራሁትን ሁሉ ኃጢአት አንተ ታውቀዋለህ ኩላሊትንም ልቡናንም የምትመረምር አንተ ነህ ሠውሬ የሠራሁትን የሥራዬን ክፋት አንተ ታውቀዋለህ ክፉ ሥራዬን አይተህ በኔ ለመፍረድ የማትቸኩል ከተድላዬ የማታዋርደኝ አንተ ነህ በወደቅሁም ጊዜ አካሄዴን የማታዋርድ
አንተ ነህ በጎ አድራጊ ይቅር ባይ ሆይ አትቸኩልም አንተስ መመለሴንም እየጠበቅህ ትዕግስትህን አበዛህልኝ  እኔም ከእንቅልፌ ነቅቼ ይቅርታህን ስፈልግ ወዳንተ ገሠገሥኩ ንስሐ የሚገባውን ሰው ንስሐውን እንድትቀበው አውቄ ባለኝታህ ጸንቼ ወዳንተ ገሠገሥኩ የተናቅሁ ድሀ እኔ እለምንሃለሁ ከወደቅሁበት ታነሣኝ ዘንድ ኃጢአቴንም ትተላለፋት  ዘንድ ንስሐዬንም ትቀበለኝ ዘንድ ከመዓርጌ አዋርዶ ስለጣለኝ ጠላት እንዳይመካ ሳትነፍግ ሳትሳሳ የምትሰጥ በጎ አሳቢ ቸር ጌታችን ፈጣሪያችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ አንተ በታመነ ቃላህ በክቡር ወንጌልህ እሹ ታገኛላችሁ ለምኑ ይሰጣችል ደጅ ምቱ ይከፈትላችል ብለህ ተናግረሃል (ማቴ ፯፡፯)
አቤቱ ችጋረኛ ድሀ የምሆን እኔም እውነተኛ ነገርህን አለኝታ ተቀብዬ በቃለህ ጸንቼ ኃጢአቴን አምኜ እየማለድሁ እነሆ በፊትህ ቆሜ አለሁ፡፡
ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ አለኝታዬን ቆርጠህ እንዳታሳፍረኝ እለምንሃለሁ በደካማነቴ ራርተህ ኃጢአቴን ይቅር ትለኝ ዘንድ ፊትህንም ከኔ እናዳትመልስ ያን ጊዜ አንተን ለመለመን የማልበቃ ኃጥእ በደለኛ እሆናለሁ ያደፍኩ የረከስኩ ነኝና፡፡
ነገር ግን በይቅርታህና በቸርነትህ ብዛት የፍጥረትህን ዕርቅና መዳንን በመውደድህ ነገሬን መልስልኝ ልቅሶዬንም ተቀበለኝ ጌታዬ ፈጣሪዬ ሆይ የሥራዬን ክፋት የኃጢአቴን ብዛት አይተህ ዕንባዬን አታሳፍረኝ እንደ እውነተኛ አለኝታህ በክቡር  ስምህ እንደማመኔ ይደረግልኝ እንጂ የነጻች የእጅህ ሥራ የምሆን  እኔ ከባሮችህ ወገን ነኝና እኔም በክቡር ምሳሌህና በመልክህ ተፈጥሬ አለሁና በጥበብህ ከፈጠርኻቸው ከባሮችህ ወገን ስለሆንኩ ስለዚህ ደፍሬ የረከሰች አንደበቴን ገልጨ እለምንሃለሁ፡፡
ኃጢአቴን ይቅር ትለኝ ዘንድ ንስሐዬንም ትቀበለኝ ዘንድ ጽኑዕ ሥልጣን ከሃሊነት ያለህ ቸር ሆይ ጎስላ ድሀ የምሆን እኔን በይቅርታህ እንድታድነኝ በቸርነትህ ታደገኝ የበዛች ኃጢአቴንም በደሌንም አርቅልኝ እኔ የተከዝኩ በደለኛ ነኝና፡፡
አቤቱ በምለምንህ ጊዜ ፊትህን ከኔ ከባርያህ አትመልስ አቤቱ ወዳንተ በለመንሁ ጊዜ ይቅርታህን አታርቅብኝ የጌቶች ጌታ የንጉሶች ንጉሥ ሆይ ወደ አንተ የሚመላለሱትን ዕርቅ ትወዳለህና የሥጋና የነፍስን ደኅንነትንም ትወዳለህና፡፡
ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የቀናች ሃይማኖትንና እውነተኛ መመነስን ስጠኝ የጸራች ንስሐንም ትሰጠኝ ዘንድ እለምንሃንሁ፡፡የሚጠሉኝ ጠላቶቼ የክፉ አጋንንት ድንገት በሚመጡበት ጊዜ ወደ አድነኝ ነፍሴ ከሥጋዬ በምትለይበት ጊዜ ወደ አንተ አቅርበኝ እንጂ ካንተ ወደ ሌላ አሳልፈህ አትስጠኝ ሁሉ የሚቻልህ ፈጣሪ ሆይ ጠላቶቼን በኔ አታሠልጥናቸው አታሰናብታቸውም፡፡
ፈጣሪ ጌታ አዛኝ ይቅር ባይ ሆይ የይቅርታና የቅንነት ሣጥን እግዚአብሔር ሆይ ሕይወትን የምትሰጥ በጎ ነገርን የምትወድ አንተ ነህና ስለዚህ ከክፉ ጠላቶቼ አድነኝ እሳቸውን ከመፍራት የተነሣ ነፍሴ ትንቀጠቀጣለችና ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ያለክቡር ስምህና ያለ አንተ ለዘላለሙ ድኅነት የለኝም አሜን በእውነት፡፡
መዝሙረ ዳዊት 6

1 አቤቱ፥ በቍጣህ አትቅሠፈኝ፥ በመዓትህም አትገሥጸኝ።
2 ድውይ ነኝና አቤቱ፥ ማረኝ አጥንቶቼ ታውከዋልና ፈውሰኝ።
3 ነፍሴም እጅግ ታወከች አንተም አቤቱ፥ እስከ መቼ ድረስ ነው?
4 አቤቱ፥ ተመለስ ነፍሴንም አድናት፥ ስለ ቸርነትህም አድነኝ።
5 በሞት የሚያስብህ የለምና፥ በሲኦልም የሚያመሰግንህ ማን ነው?
6 በጭንቀቴ ደክሜያለሁ ሌሊቱን ሁሉ አልጋዬን አጥባለሁ፥ በዕንባዬም መኝታዬን አርሳለሁ።
7 ዓይኔ ከቍጡ ዕንባ የተነሣ ታወከች ከጠላቶቼ ሁሉ የተነሣ አረጀሁ።
8 ዓመፃን የምታደርጉ ሁሉ፥ ከእኔ ራቁ፥ እግዚአብሔር የልቅሶዬን ቃል ሰምቶአልና።
9 እግዚአብሔር ልመናዬን ሰማኝ እግዚአብሔር ጸሎቴን ተቀበለ።
10 ጠላቶቼ ሁሉ ይፈሩ እጅግም ይጐስቍሉ ወደ ኋላቸው ይመለሱ፥ በፍጥነትም ይፈሩ።





1 አስተያየት:

  1. ቃለ ህይወት ያሰማልን!
    ጥያቂ: ውዳሴ አምላክን ማን ነው የተረጎመው?

    ምላሽ ይስጡሰርዝ